ከኢየሱስ ተማሩ
“ጦርነትና የጦርነት ወሬ ትሰማላችሁ”
“ከ1960ዎቹ አንስቶ በዚህ ሙያ ላይ ባሳለፍኳቸው ዓመታት ከ40 በላይ ጦርነቶችን ዘግቤያለሁ። ቀዝቃዛው ጦርነት ሲፋፋም፣ ከዚያም እንደ ጉም በንኖ ሲጠፋ ተመልክቻለሁ። እንደ 2025 ግን ስጋት የፈጠረብኝ ዓመት የለም፤ ዓለማችን ጥቂት በማይባሉ ትላልቅ ጦርነቶች መታመሷ ብቻ አይደለም ያሳሰበኝ፤ ከዚህ ይልቅ ከእነዚህ ጦርነቶች አንዱ፣ ዓለም ላይ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ጂኦ ፖለቲካዊ አንድምታ ያለው መሆኑም ጭምር ነው።”—ጆን ሲምፕሰን፣ የቢቢሲ የዓለም ጉዳዮች ዘጋቢ (ደመቅ አድርገን የጻፍነው እኛ ነን)
ዓለምን እየተፈታተኗት ያሉትን ጦርነቶች ሲያስቡ ብዙዎች ይሰጋሉ። እነዚህ ጦርነቶች ማብቂያ ይኖራቸው ይሆን? ኢየሱስ ምን አስተምሯል?
ኢየሱስ ምን አስተምሯል?
ኢየሱስ ዛሬ የምናያቸው ነገሮች በዓለም ላይ እንደሚከሰቱ አስቀድሞ ተናግሯል። “ጦርነትና የጦርነት ወሬ ትሰማላችሁ” በማለት ተከታዮቹን አስጠንቅቋል።—ማቴዎስ 24:6
ዛሬ የምናያቸው ጦርነቶችና ግጭቶች ቢያስጨንቁንም ነገን በተስፋ የምንጠብቅበት ምክንያት አለን። ለምን? ምክንያቱም ኢየሱስ ትላልቅ ጦርነቶችን ጨምሮ ሌሎች ክስተቶችን በመዘርዘር “የዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ምልክት” እንደሆኑ አስተምሯል። (ማቴዎስ 24:3፤ ሉቃስ 21:7) ስለዚህ ኢየሱስ ጦርነትን የሚያስቀርበት ጊዜ ቀርቧል ማለት ነው። ይህ የሚሆነው እንዴት ነው?
በቅርቡ ኢየሱስ ምን ያደርጋል?
ኢየሱስ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ ነው፤ በቅርቡ “ጦርነትን ከመላው ምድር ላይ ያስወግዳል።”—መዝሙር 46:9
ታዲያ መጪው ጊዜ ምን ይመስላል? በምድር ላይ ሰላም የሚሰፍነው እንዴት ነው? የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ማወቅ ከፈለግህ “ጦርነት እና ግጭት የሚቀረው እንዴት ነው?” የሚለውን ርዕስ አንብብ።