ረቡዕ፣ ሚያዝያ 15
እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ።—ዮሐ. 15:12
የይሖዋ ሕዝቦች እርስ በርስ መረዳዳት ያስደስታቸዋል። (2 ቆሮ. 8:4) ይሁንና አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ማድረግ ድፍረት ይጠይቃል። ለምሳሌ ጦርነት በሚቀሰቀስበት ጊዜ የጉባኤ ሽማግሌዎች ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ማበረታቻ፣ ድጋፍ እንዲሁም መንፈሳዊ ምግብና ቁሳዊ እርዳታ ሊያስፈልጋቸው እንደሚችል ይገነዘባሉ። ሽማግሌዎች ለመንጋው ፍቅር ስላላቸው የራሳቸውን ደህንነት አደጋ ላይ መጣል ቢጠይቅባቸውም እንኳ ወንድሞቻቸው የሚያስፈልጋቸውን ነገር ያቀርባሉ። እንዲህ ባሉት ሁኔታዎች ውስጥ ስንሆን አንድነታችንን መጠበቃችን በጣም አስፈላጊ ነው። ከቅርንጫፍ ቢሮው ያገኘኸውን መመሪያ ተከተል። (ዕብ. 13:17) ሽማግሌዎች ለአደጋ ከመዘጋጀት እንዲሁም አደጋ ሲከሰት መወሰድ ካለባቸው እርምጃዎች ጋር በተያያዘ ያሉትን መመሪያዎች አዘውትረው መከለስ ይኖርባቸዋል። (1 ቆሮ. 14:33, 40) ደፋር ሆኖም ጠንቃቃ ሁን። (ምሳሌ 22:3) የማመዛዘን ችሎታህን ተጠቀም። ሳያስፈልግ ራስህን አደጋ ላይ አትጣል። በይሖዋ ታመን። ይሖዋ ደህንነትህን አደጋ ላይ ሳትጥል ወንድሞችህን እንድትደግፍ ሊረዳህ ይችላል። w24.07 4 አን. 8፤ 5 አን. 11
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 16
በጭንቅ ውስጥ ሳለሁ ይሖዋን ጠራሁት፤ . . . እርዳታ ለማግኘት የማሰማውም ጩኸት ወደ ጆሮው ደረሰ።—መዝ. 18:6
ንጉሥ ዳዊት ይሖዋን ያውቀውና ይታመንበት ነበር። ንጉሥ ሳኦልን ጨምሮ ጠላቶቹ ሲያሳድዱት ዳዊት ይሖዋ እንዲረዳው ጸልዮአል። አምላክ ጸሎቱን በመስማት ከታደገው በኋላ ዳዊት “ይሖዋ ሕያው ነው!” በማለት ስሜቱን ገልጿል። (መዝ. 18:46) ዳዊት ይህን ሲል አምላክ መኖሩን መናገሩ ብቻ አልነበረም። አንድ የማመሣከሪያ ጽሑፍ እንደሚገልጸው ዳዊት ይህን ሲል ይሖዋ “ሕዝቦቹን ለመርዳት ሁልጊዜ እርምጃ የሚወስድ ሕያው አምላክ መሆኑን” በእርግጠኝነት እንደሚያምን መናገሩ ነው። አዎ፣ ዳዊት አምላኩ ሕያው መሆኑን በገዛ ሕይወቱ አይቷል፤ ይህ እምነቱ ደግሞ ይሖዋን ለማገልገልና ለማወደስ ያለውን ቁርጠኝነት አጠናክሮለታል። (መዝ. 18:28, 29, 49) ይሖዋ ሕያው አምላክ እንደሆነ ማመናችን እሱን በቅንዓት ለማገልገል ይረዳናል። ፈተናዎችን በጽናት ለመቋቋም የሚያስችል ብርታትና አምላክን በትጋት ማገልገላችንን ለመቀጠል የሚያስችል ተነሳሽነት ይኖረናል። ከዚህም ሌላ፣ ከይሖዋ ጋር ተቀራርበን ለመኖር ያለንን ቁርጠኝነት ያጠናክርልናል። w24.06 20-21 አን. 3-4
ዓርብ፣ ሚያዝያ 17
ማንም ሰው በምንም መንገድ አያሳስታችሁ።—2 ተሰ. 2:3
ሐዋርያው ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ከተናገረው ሐሳብ ምን እንማራለን? ከመጽሐፍ ቅዱስ ከተማርናቸው እውነቶች ጋር የማይስማማ ነገር ወይም አስደንጋጭ ወሬ ስንሰማ የማስተዋል ችሎታችንን መጠቀም ይኖርብናል። በቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት ውስጥ ጠላቶቻችን ከዋናው መሥሪያ ቤት የተላከ የሚመስል ደብዳቤ አሰራጭተው ነበር። ደብዳቤው አንዳንድ ወንድሞች የራሳቸውን ድርጅት እንዲያቋቁሙ የሚያበረታታ ነበር። ደብዳቤው ሲታይ እውነተኛ ይመስላል። ታማኝ የሆኑ ወንድሞች ግን በዚህ አልተታለሉም። ደብዳቤው የያዘው መልእክት አስቀድመው ከተማሯቸው ነገሮች ጋር እንደማይስማማ አስተዋሉ። ዛሬም የእውነት ጠላቶች አንዳንድ ጊዜ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ግራ እንድንጋባና በመካከላችን መከፋፈል እንዲፈጠር ለማድረግ ይጥራሉ። ‘የማመዛዘን ችሎታችን በቀላሉ እንዲናወጥ’ ከመፍቀድ ይልቅ የሰማነው ወይም ያነበብነው ነገር ከተማርናቸው እውነቶች ጋር የሚስማማ መሆን አለመሆኑን በመመዘን ራሳችንን መጠበቅ እንችላለን።—2 ተሰ. 2:2፤ 1 ዮሐ. 4:1፤ w24.07 12 አን. 14-15