የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • w26 የካቲት ገጽ 26-29
  • “ልጆች ከይሖዋ የተገኙ ውርሻ ናቸው”

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • “ልጆች ከይሖዋ የተገኙ ውርሻ ናቸው”
  • የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ (የጥናት እትም)—2026
  • ንዑስ ርዕሶች
  • ተመሳሳይ ሐሳብ ያለው ርዕስ
  • አንዳንድ ወላጆች ብዙ ልጆች የሚወልዱት ለምንድን ነው?
  • ይሖዋ ወላጆች ምን እንዲያደርጉ ይጠብቅባቸዋል?
  • ይሖዋ እንዲሳካላችሁ ይፈልጋል
  • ወላጆች፣ ልጆቻችሁ ይሖዋን እንዲወዱ አሠልጥኗቸው
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ (የጥናት እትም)—2019
  • ወላጆች፣ ልጆቻችሁ ይሖዋን እንዲወዱ እርዷቸው
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ (የጥናት እትም)—2022
  • ወላጆች፣ የቤተሰባችሁን ፍላጎት አሟሉ
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ—2005
  • በመንፈሳዊ ጠንካራ የሆነ ቤተሰብ መገንባት
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ—2001
ለተጨማሪ መረጃ
የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ (የጥናት እትም)—2026
w26 የካቲት ገጽ 26-29
አንድ አባትና እናት ሴት ልጃቸውን አቅፈው፤ ሁሉም ደስተኛ ናቸው።

“ልጆች ከይሖዋ የተገኙ ውርሻ ናቸው”

“ውርሻ” የሚለውን ቃል ስትሰማ ወደ አእምሮህ የሚመጣው ምንድን ነው? አንድ የቤተሰብህ አባል ያወረሰህን ገንዘብ፣ ንብረት ወይም ውድ ቅርስ ታስብ ይሆናል። ያገኘኸው ውርስ ምንም ይሁን ምን፣ ውድ አድርገህ እንደምትመለከተውና በጥንቃቄ ለመያዝ ጥረት እንደምታደርግ ምንም ጥያቄ የለውም።

መጽሐፍ ቅዱስ “ልጆች ከይሖዋ የተገኙ ውርሻ ናቸው” ይላል። (መዝ. 127:3) ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸውን ከሰማዩ አባታቸው ያገኟቸው ውድ ስጦታዎች እንደሆኑ አድርገው ይመለከቷቸዋል። በመሆኑም እነሱን ከጉዳት ለመጠበቅ እንዲሁም አካላዊ፣ ስሜታዊና መንፈሳዊ ፍላጎታቸውን ለማሟላት የተቻላቸውን ሁሉ ጥረት ያደርጋሉ።

የሚያሳዝነው ግን፣ በዛሬው ጊዜ ያሉ አንዳንድ ወላጆች ልጆቻቸውን ከአምላክ እንደተገኙ ስጦታዎች አድርገው አይመለከቷቸውም። (ኢሳ. 49:15፤ 2 ጢሞ. 3:1-3) ሌሎች ደግሞ ልጆቻቸውን የመንከባከብ ልባዊ ፍላጎት ቢኖራቸውም ብዙ ልጆች ስላሏቸው እንዲህ ለማድረግ ይቸገራሉ። ወላጆች ተንከባክበው ሊያሳድጉ ከሚችሉት በላይ ብዙ ልጆችን እንዲወልዱ የሚያደርጋቸው ምን ሊሆን ይችላል? ይሖዋ ወላጆች ምን እንዲያደርጉ ይጠብቅባቸዋል? ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸውን ጥሩ አድርገው ማሳደግ የሚችሉትስ እንዴት ነው?

አንዳንድ ወላጆች ብዙ ልጆች የሚወልዱት ለምንድን ነው?

  • ቤተሰብና ማኅበረሰቡ የሚያሳድረው ተጽዕኖ። በአንዳንድ አገሮች፣ ብዙ ልጆች ያሏቸው ወላጆች በማኅበረሰቡ ዘንድ ከፍ ያለ ክብር ያገኛሉ። በመሆኑም ባለትዳሮች ማሳደግ ከሚችሉት በላይ ብዙ ልጅ እንዲወልዱ በዘመዶቻቸው ወይም በጎረቤቶቻቸው ጫና ይደረግባቸዋል።

  • ስለ ወደፊቱ ጊዜ መጨነቅ። በአንዳንድ አገሮች በምግብ እጥረት፣ በበሽታና በጤና አገልግሎት ውስንነት የተነሳ በርካታ ልጆች በጨቅላነታቸው ይሞታሉ። በእነዚህ አገሮች የሚኖሩ ወላጆች ‘ቢያንስ የተወሰኑት ያድጉልኝ ይሆናል’ ብለው በማሰብ በርካታ ልጆችን ይወልዳሉ። ሌሎች ባለትዳሮች ደግሞ ዕድሜያቸው ሲገፋ የሚጦራቸው እንዳያጡ በመስጋት ብዙ ልጆችን ለመውለድ ይወስኑ ይሆናል። በተለይ መንግሥት ለአረጋውያን ምንም ዓይነት ድጋፍ በማያደርግባቸው አገሮች ውስጥ እንዲህ ማድረግ የተለመደ ነው።

  • የቤተሰብ ምጣኔ። በአንዳንድ አካባቢዎች የሚኖሩ ባለትዳሮች የወሊድ መቆጣጠሪያ ለማግኘት ይቸገራሉ። ሌሎች ደግሞ ማግኘት የሚችሉት ዝቅተኛ የጥራት ደረጃ ያለውን የወሊድ መቆጣጠሪያ ብቻ ስለሆነ የጎንዮሽ ጉዳቱን ይፈራሉ። የወሊድ መቆጣጠሪያ ለመጠቀም የገንዘብ አቅማቸው የማይፈቅድላቸውም አሉ።a

ይሖዋ ወላጆች ምን እንዲያደርጉ ይጠብቅባቸዋል?

አንድ ቤተሰብ መናፈሻ ውስጥ አብረው ሲዝናኑ። አባትየው በአሥራዎቹ ዕድሜ የምትገኘውን ልጁን በጥሞና እያዳመጣት ነው፤ እናትየዋ ደግሞ ከታናሹ ልጅ ጋር ኳስ እየተጫወተች ነው።

ከእያንዳንዱ ልጅ ጋር ጊዜ አሳልፉ

ልጆቻቸው የሚያስፈልጋቸውን ቁሳዊ ነገር እንዲያሟሉ። ይሖዋ ወላጆች ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆቻቸውን ቁሳዊ ፍላጎት እንዲያሟሉ ኃላፊነት ሰጥቷቸዋል። ይሖዋ ወላጆች ለእያንዳንዱ ልጃቸው ምግብ፣ ልብስና መጠለያ ለማቅረብ ጠንክረው እንዲሠሩ ይጠብቅባቸዋል። በተጨማሪም ይሖዋ፣ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዲያስተምሯቸው ይፈልጋል። በመሆኑም ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ አዳሪ ትምህርት ቤት ልከው ከዚህ ኃላፊነት ነፃ ለመውጣት አይሞክሩም። ከዚህ ይልቅ ልጆቻቸው እስኪያድጉ ድረስ አብረዋቸው እንዲኖሩና አስፈላጊውን የቀለም ትምህርት እንዲያገኙ ያደርጋሉ፤ በተጨማሪም ለልጆቻቸው በግለሰብ ደረጃ ትኩረት ይሰጧቸዋል። ይህም ልጆቹ የሚያስፈልጋቸውን ፍቅርና እንክብካቤ አግኝተው እንዲያድጉ ያስችላል። ያም ሆኖ ይሖዋ ምክንያታዊ ነው፤ ወላጆች ሀብታም እንዲሆኑ አይጠብቅባቸውም። እንዲያውም ይሖዋ የሚወደውን ልጁን እንዲያሳድጉ የመረጣቸው ሰዎች ታታሪ ሆኖም ድሃ ነበሩ።—ማቴ. 13:55, 56፤ ሉቃስ 2:24

የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓት፦ “በእርግጥም አንድ ሰው የራሱ ለሆኑት በተለይ ደግሞ ለቤተሰቡ አባላት የሚያስፈልጋቸውን ነገር የማያቀርብ ከሆነ እምነትን የካደ ከመሆኑም በላይ እምነት የለሽ ከሆነ ሰው የከፋ ነው።”—1 ጢሞ. 5:8

ይሖዋ ወላጆች በዕድሜ ሲገፉ እርዳታ ሊያስፈልጋቸው እንደሚችል ያውቃል። እንዲያውም ልጆች ወላጆቻቸውን እንደሚያከብሩ የሚያሳዩበት አንዱ መንገድ ወላጆቻቸው በዕድሜ ሲገፉ እንክብካቤ የሚያገኙበትን መንገድ በማመቻቸት ነው። (ዘፀ. 20:12፤ 1 ጢሞ. 5:4) ሆኖም ወላጆች ‘ልጆቼ ወደፊት እኔን እንዴት ይንከባከቡኛል?’ ከሚለው ጉዳይ ይልቅ ‘እኔ ልጆቼን መንከባከብ የምችለው እንዴት ነው?’ በሚለው ላይ ትኩረት ሲያደርጉ ይሖዋ ይደሰታል።—2 ቆሮ. 12:14

የልጆቻቸውን መንፈሳዊ ፍላጎት እንዲያሟሉ። ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸው ይሖዋን እንዲወዱና እንዲያመልኩት የማሠልጠን ኃላፊነትም አለባቸው። እንዲያውም በይሖዋ አመለካከት፣ ወላጆች ለልጆቻቸው ሊሰጡ የሚችሉት ትልቁ ነገር እንዲህ ያለው መንፈሳዊ ሥልጠና ነው።—ዘዳ. 6:6, 7

የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓት፦ “ልጆቻችሁን . . . በይሖዋ ተግሣጽና ምክር አሳድጓቸው።”—ኤፌ. 6:4

ይሖዋ እንዲሳካላችሁ ይፈልጋል

አንድ ባልና ሚስት ቤታቸው ውስጥ ሆነው ሲወያዩ። ከፊታቸው ባለው ጠረጴዛ ላይ የተገለጠ መጽሐፍ ቅዱስ አለ።

ስንት ልጆች መውለድ እንደምትፈልጉ አስቀድማችሁ ተወያዩ

አስቀድማችሁ ዕቅድ አውጡ። ልጆች ለመውለድ እያሰባችሁ ከሆነ ሁኔታችሁን በጥንቃቄ ገምግሙ። ለምሳሌ ብዙ ልጆችን ለመመገብ፣ ለማልበስና ለማስተማር የገንዘብ አቅማችሁ ይፈቅድላችኋል? ካልሆነ፣ ከትዳር አጋራችሁ ጋር በመመካከር ይሖዋ በሚጠብቅባችሁ መጠን ተንከባክባችሁ ማሳደግ የምትችሉት ስንት ልጅ እንደሆነ ወስኑ። እርግጥ ይሖዋ ሁሉም ነገር ባቀድነው መሠረት እንደማይሄድ ያውቃል። (መክ. 9:11) ሆኖም ልጆቻችሁን ጥሩ አድርጋችሁ ለማሳደግ የምታደርጉትን ልባዊ ጥረት ይባርክላችኋል።

የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች፦ “የትጉ ሰው ዕቅድ ለስኬት ያበቃዋል፤ ችኩሎች ሁሉ ግን ለድህነት ይዳረጋሉ።”—ምሳሌ 21:5

“ከእናንተ መካከል፣ ግንብ ለመገንባት ፈልጎ ለመጨረስ የሚያስችል በቂ ገንዘብ እንዳለው ለማወቅ በመጀመሪያ ተቀምጦ ወጪውን የማያሰላ ማን ነው?”—ሉቃስ 14:28

በቤተሰባችሁ ውስጥ ይሖዋን አስቀድሙ። ቤተሰባችሁ ለይሖዋ አምልኮ ቅድሚያ እንዲሰጥ አድርጉ። ልጆች ካሏችሁ ለእያንዳንዱ ልጃችሁ ጊዜ ሰጥታችሁ ይሖዋን እንዲወድ ለማስተማር ጥረት አድርጉ። ልጆቻችሁ በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በትኩረት እንዲከታተሉና እንዲማሩ እርዷቸው። ቋሚ የቤተሰብ አምልኮ ፕሮግራም ይኑራችሁ። ልጆቻችሁን በአገልግሎት ረገድ አሠልጥኗቸው። ወላጅ እንደመሆናችሁ መጠን፣ እነዚህን ነገሮች ማድረግ የእናንተ ኃላፊነት ነው፤ ትላልቆቹ ልጆቻችሁ ወይም ሌሎች ዘመዶቻችሁ በእናንተ ፋንታ እነዚህን ነገሮች እንዲያደርጉላችሁ አትጠብቁ። ልጆች ይሖዋን እንዲወዱ አድርጎ ማሳደግ ጊዜና ጥረት ቢጠይቅም በእጅጉ የሚክስ ነው።

የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓት፦ “ልጆቼ በእውነት ውስጥ እየተመላለሱ መሆናቸውን ከመስማት የበለጠ ደስታ የለኝም።”—3 ዮሐ. 4b

በይሖዋ ታመኑ። ልጆች ለመውለድ እያሰባችሁ ከሆነ ወይም ልጆች ካሏችሁ ከአካባቢያችሁ ባሕል ወይም ልማድ ይልቅ የይሖዋ መሥፈርቶች ቅድሚያ ሊሰጣቸው እንደሚገባ አስታውሱ።

ሥዕሎች፦ 1. አንድ አባትና እናት በጉባኤ ስብሰባ ላይ ከልጃቸው ጋር አብረው ተቀምጠዋል። ልጁ መልስ ለመመለስ እጁን አውጥቷል። 2. የአንድ ቤተሰብ አባላት አብረው ሲያገለግሉ። አባትየው ከትልቋ ልጅ ጋር እያገለገለ ነው፤ እናትየው ደግሞ ከሁለቱ ታናናሽ ልጆች ጋር ታገለግላለች።

የልጆችን መንፈሳዊ ፍላጎት ማሟላት ጊዜና ጥረት ይጠይቃል

ብዙ ልጆችን ላለመውለድ ብትወስኑም እንኳ ይሖዋ ዕድሜያችሁ ሲገፋ እንደሚደግፋችሁ ተማመኑ። አንዳንዶች እንደሚያደርጉት፣ ልጆችን እንደ “ጡረታ ዋስትና” አድርጋችሁ ከመመልከት ተቆጠቡ። ዕድሜያችሁ ሲገፋ የሚንከባከባችሁ እንደማይኖር በማሰብ ፈጽሞ ልትጨነቁ አይገባም። ይሖዋ እንደሚንከባከባችሁ ቃል ገብቷል፤ እሱ ደግሞ መቼም ቢሆን ቃሉን አያጥፍም።—ኢያሱ 23:14

የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች፦ “በሙሉ ልብህ በይሖዋ ታመን፤ ደግሞም በገዛ ራስህ ማስተዋል አትመካ። በመንገድህ ሁሉ እሱን ግምት ውስጥ አስገባ፤ እሱም ጎዳናህን ቀና ያደርገዋል።”—ምሳሌ 3:5, 6

“በአንድ ወቅት ወጣት ነበርኩ፤ አሁን ግን አርጅቻለሁ፤ ይሁንና ጻድቅ ሰው ሲጣል፣ ልጆቹም ምግብ ሲለምኑ አላየሁም።”—መዝ. 37:25

“እንግዲያው ከሁሉ አስቀድማችሁ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ ፈልጉ፤ እነዚህም ነገሮች ሁሉ ይሰጧችኋል።”—ማቴ. 6:33

ልጆች ይሖዋ ለወላጆች በአደራ የሰጣቸው ውድ ስጦታዎች ናቸው። ክርስቲያን ባለትዳሮች ይህን አደራ ሲወጡ ይሖዋ ምንኛ ይደሰት ይሆን! ከአካባቢያቸው ባሕል ወይም ልማድ ይልቅ ይሖዋ ለሚጠብቅባቸው ነገር ቅድሚያ ይሰጣሉ። በመሆኑም ስንት ልጆች እንደሚወልዱ በጥንቃቄ ይወስናሉ። እንዲሁም የልጆቻቸውን አካላዊ፣ ስሜታዊና መንፈሳዊ ፍላጎቶች ለማሟላት ልባዊ ጥረት ያደርጋሉ። ክርስቲያን ወላጆች እንዲህ በማድረግ ልጆቻቸውን ‘ከይሖዋ የተገኙ ውርሻ’ አድርገው እንደሚመለከቷቸው ያሳያሉ።

በውሳኔያቸው አልተቆጩም

አንድ አባት ለሚስቱና ለሁለት ትናንሽ ልጆቹ የቤተሰብ አምልኮ ሲመራ።

ወላጆች ብዙ ልጆች ላለመውለድ ከወሰኑ ለችግር ይዳረጋሉ? የኢኮኖሚ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ብዙ ወላጆች ይህ ጥያቄ ያሳስባቸዋል። በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖሩ አንዳንድ አባቶች ስለዚህ ጉዳይ ምን እንዳሉ ልብ በሉ።

ብዙ ልጆች እንድትወልዱ ጫና ተደርጎባችሁ ነበር?

“አዎ፣ በጉባኤ ውስጥ ካሉ አንዳንድ ሰዎችም ጭምር ጫና ደርሶብናል። አንድ ባልና ሚስት እንዲህ ብለውናል፦ ‘አንድ ልጅ ብቻ የወለዳችሁት ለምንድን ነው? አፍሪካ ውስጥ እኮ አንድ ልጅ ካላችሁ ምንም ልጅ እንደሌላችሁ፣ ሁለት ልጅ ካላችሁ ደግሞ አንድ ልጅ እንዳላችሁ ነው የሚቆጠረው።’ ሁለተኛ ልጃችን ከተወለደች በኋላም የሚደርስብን ጫና አላቆመም።”—ዤረሚያስ

ብዙ ልጆች ባለመውለዳችሁ ምክንያት ቁሳዊ ወይም መንፈሳዊ ጉዳት ደርሶባችኋል?

“በፍጹም። እንዲያውም የሆነው ተቃራኒው ነው። እኔና ባለቤቴ ብዙ ልጆች ላለመውለድ በመወሰናችን ቁሳዊ ፍላጎታችንን፣ ከሁሉ በላይ ደግሞ መንፈሳዊ ፍላጎታችንን በተሻለ ሁኔታ ማሟላት ችለናል። ያደግኩት በትልቅ ቤተሰብ ውስጥ ነው። በመሆኑም ወላጆቻችን የሚያስፈልገንን ነገር ለማሟላትና እኛን ትምህርት ቤት ለመላክ ብዙ ችግር ሲያዩ ተመልክቻለሁ።”—ዤረሚያስ

ልጆቻችሁ ያደረጋችሁትን ውሳኔ በተመለከተ ምን ይሰማቸዋል?

“ልጆቻችን ሌሎች ልጆች ወላጆቻቸው ብዙ ልጆች በመውለዳቸው ምክንያት የሚያስፈልጋቸውን እንክብካቤ እንደማያገኙ ይመለከታሉ፤ እነሱ እንዲህ ላሉት ችግሮች ስላልተዳረጉ ደስተኞች ናቸው።”—ፊሊፔ

“ልጆቻችን ፍቅር በሰፈነበት ቤት ውስጥ የሚያስፈልጋቸውን እንክብካቤ አግኝተው በማደጋቸው ደስተኞች ናቸው። በመንፈሳዊ የጎለመሱ ወንድሞችና እህቶችን ሁልጊዜ ቤታችን እንጋብዝ ነበር፤ እነሱም መንፈሳዊ ግቦችን እንድናወጣ አበረታተውናል። የጥረታችንን ፍሬ ዛሬ በልጆቻችን ላይ እያየን ነው።”—ካርሎስ

ብዙ ልጆች ላለመውለድ በመወሰናችሁ ያገኛችሁት ጥቅም አለ?

“ውሳኔያችን ቤተሰባችንን በተሻለ ሁኔታ ለማስተዳደር አስችሎናል። ከሦስት ዓመት በፊት ጥሩ ደሞዝ የሚያስገኝ ሥራዬን አጥቼ ነበር። ሆኖም የቤተሰባችን ቁጥር ትንሽ ስለነበር የሚያስፈልገንን ነገር ለማሟላት ብዙ ገንዘብ አላስፈለገንም። ይህም ለውጡን ማስተናገድ ቀላል እንዲሆንልን አድርጓል።”—ዤረሚያስ

“ያደረግነው ውሳኔ የልጆቻችንን ቁሳዊም ሆነ መንፈሳዊ ፍላጎት ለማሟላት አስችሎናል። እርዳታ በሚያስፈልግባቸው ቦታዎች ማገልገል ችለናል። እያንዳንዱ ልጅ የሚያስፈልገውን ነገር ማሟላት ቀላል ሆኖልናል። ልጆቻችን በሙሉ ይሖዋን እያገለገሉ ነው፤ እንዲሁም መንፈሳዊ ግቦች ላይ መድረስ ችለዋል።”—ሌናዲ

ለሌሎች ወላጆች ምን ሐሳብ ማካፈል ትፈልጋላችሁ?

“በመዝሙር 34:10ለ ላይ የሚገኘው ሐሳብ እውነት መሆኑን በሕይወቴ ተመልክቻለሁ፤ ጥቅሱ እንዲህ ይላል፦ ‘ይሖዋን የሚሹ . . . መልካም ነገር አይጎድልባቸውም።’ ይሖዋ እኔና ቤተሰቤ የሚያስፈልገንን ነገር በሙሉ አሟልቶልናል።”—ራፋኤል

a ባለትዳሮች ስንት ልጆች እንደሚወልዱ፣ መቼ እንደሚወልዱ እንዲሁም የወሊድ መቆጣጠሪያ መጠቀም ይኖርባቸው እንደሆነና እንዳልሆነ በራሳቸው መወሰን ይኖርባቸዋል። በሚያደርጉት የግል ውሳኔ የተነሳ ማንም ሰው በእነሱ ላይ ሊፈርድ አይገባም። (ሮም 14:4, 10-13) እርግጥ የሚጠቀሙበት የወሊድ መቆጣጠሪያ ዘዴ ፅንስ የሚያቋርጥ ሊሆን አይገባም። በተጨማሪም ያገቡ ክርስቲያኖች በ1 ቆሮንቶስ 7:3-5 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘውን ምክር ማስታወስ ይኖርባቸዋል።

b ዮሐንስ እዚህ ላይ “ልጆቼ” ያለው እውነትን ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ቢሆንም ወላጆች ልጆቻቸው ይሖዋን ሲያገለግሉ ሲያዩ የእሱ ዓይነት ስሜት ይሰማቸዋል።

    አማርኛ ጽሑፎች (1991-2026)
    ውጣ
    ግባ
    • አማርኛ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2026 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ