የአንባቢያን ጥያቄዎች
ሐዋርያው ጳውሎስ በገላትያ 4:24 ላይ የተናገረው ስለ የትኞቹ ሁለት ቃል ኪዳኖች ነው?
ሐዋርያው ጳውሎስ፣ አብርሃም ከሣራና ከአጋር ጋር ስለነበረው ግንኙነት ከተናገረ በኋላ እንዲህ ብሏል፦ “እነዚህ ሴቶች ሁለት ቃል ኪዳኖችን ስለሚወክሉ እነዚህ ነገሮች ምሳሌያዊ ትርጉም አላቸው።” (ገላ. 4:22-24) ቀደም ሲል፣ እዚህ ላይ የተጠቀሱት ሁለት ቃል ኪዳኖች የሕጉ ቃል ኪዳንና አዲሱ ቃል ኪዳን እንደሆኑ እናምን ነበር። ሆኖም በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ምርምር ካደረግን በኋላ ማስተካከያ ማድረግ እንዳለብን ተገንዝበናል። ጳውሎስ እየተናገረ የነበረው ስለ አዲሱ ቃል ኪዳን ሳይሆን ስለ አብርሃም ቃል ኪዳን ይመስላል። ጳውሎስ ያነሳቸውን አንዳንድ ሐሳቦች እስቲ እንመልከት።a
ጳውሎስ አገልጋዪቱን አጋርን ከሲና ተራራ ጋር አያይዞ ጠቅሷታል። (ገላ. 4:25) ስለዚህ አጋር በ1513 ዓ.ዓ. አምላክ በሲና ተራራ ከእስራኤላውያን ጋር የገባውን የሕጉን ቃል ኪዳን ታመለክታለች። (ዘፀ. 19:5, 6) የትኛውም ፍጹም ያልሆነ ሰው ሕጉን ፍጹም በሆነ መንገድ መጠበቅ አይችልም፤ ስለዚህ ሕጉ አይሁዳውያንን የኃጢአት ባሪያዎች እንደሆኑ ያስታውሳቸዋል። ቃል ኪዳኑ እስራኤላውያን ሕጉን ፍጹም በሆነ መንገድ መጠበቅ የሚችለውን ብቸኛውን ሰው ማለትም መሲሑን ለይተው እንዲያውቁ ይረዳቸዋል። መሲሑ ፍጹም ሕይወቱን መሥዋዕት አድርጎ ሲያቀርብ ፍጹማን ያልሆኑ ሰዎች ከኃጢአትና ከሞት ባርነት ነፃ መውጣት ቻሉ። (ገላ. 3:19, 24, 25) ኢየሱስ የአምላክን ዓላማ ከፈጸመ በኋላ ሕጉ ከአገልግሎት ውጭ ሆነ።—ሮም 10:4
ጳውሎስ በአጋርና ‘በነፃዪቱ ሴት’ በሣራ መካከል ያለውን ልዩነት ገልጿል። ሣራ ልጅ የወለደችው “በተስፋ ቃል መሠረት” ነው። (ገላ. 4:23) ይህ የተስፋ ቃል የአብርሃም ቃል ኪዳን ነው። (ገላ. 3:29፤ 4:28) ይህ ቃል ኪዳን በዘፍጥረት 22:18 ላይ ይገኛል፤ እንዲህ ይላል፦ “ቃሌን ስለሰማህ የምድር ብሔራት ሁሉ በዘርህ [በአብርሃም ዘር] አማካኝነት ለራሳቸው በረከት ያገኛሉ።”
ከአብርሃም ጋር የተገባው ቃል ኪዳን ይሖዋ በኤደን ስለሰጠው ተስፋ ተጨማሪ መረጃ ይሰጣል። (ዘፍ. 3:15) ቃል ኪዳኑ በዘፍጥረት 3:15 ላይ የተጠቀሰው “ዘር” ከአብርሃም የዘር ሐረግ እንደሚመጣ ግልጽ አድርጓል። ጳውሎስ ይህ “ዘር” በዋነኝነት የሚያመለክተው ኢየሱስ ክርስቶስን እንደሆነ ተናግሯል። ሆኖም ‘የክርስቶስ የሆኑት’ ማለትም ከእሱ ጋር አብረው በመንግሥቱ የሚገዙት 144,000 ቅቡዓንም በምሳሌያዊው ዘር ውስጥ ይካተታሉ። (ገላ. 3:16, 29፤ ራእይ 14:1-3) ይሖዋ ለአብርሃም የገባው ቃል ፍጻሜ ኢየሱስን ለሚቀበሉና ለሚታዘዙ ሁሉ ብዙ በረከቶችን ያስገኛል።
ጳውሎስ በዚህ ምሳሌያዊ ንጽጽር አማካኝነት ሊያስተምር የፈለገው ነጥብ ምንድን ነው? በዘመኑ የነበሩት አይሁዳውያን ሕጉን የሙጥኝ ብለው ከቀጠሉ እንደ አጋር በባርነት ይኖራሉ። የአብርሃም “ዘር” ዋነኛ ክፍል የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን ከተቀበሉ ግን እንደ ሣራ ነፃ ሰዎች ይሆናሉ። ከኃጢአትና ከሞት ባርነት እውነተኛ ነፃነት ያገኛሉ። (ዮሐ. 8:32-34) ኢየሱስን ካልተቀበሉ የሕጉን ቃል ኪዳን ዋነኛ ዓላማ ይስታሉ፤ ምክንያቱም የቃል ኪዳኑ ዋነኛ ዓላማ እነሱን ወደ ክርስቶስ መምራት ነው።
ጳውሎስ ከጻፈላቸው የገላትያ ክርስቲያኖች ብዙዎቹ አይሁዳውያን አልነበሩም፤ ስለዚህ በሕጉ ሥር ሆነው አያውቁም። ሆኖም ለአይሁድ እምነት የሚሟገቱ አንዳንድ ሰዎች ከአሕዛብ የመጡ ክርስቲያኖች የግርዘትን መመሪያ ጨምሮ የሙሴን ሕግ ማክበር እንዳለባቸው አጥብቀው ይከራከሩ ነበር። ጳውሎስ እነዚህ ክርስቲያኖች ክርስቶስ “ነፃ” ካወጣቸው በኋላ ወደ ሕጉ “ባርነት” ቢመለሱ ሞኝነት እንደሚሆን ገልጿል።—ገላ. 5:1, 10-14
a ይህ ሐሳብ በመጋቢት 15, 2006 መጠበቂያ ግንብ ከገጽ 10-12 ላይ በወጣው ትምህርት ላይ የተደረገ ማስተካከያ ነው።