በውድድሩ አሸንፋ ሽልማቱን አገኘች
በከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የአራተኛ ዓመት ተማሪ የሆነችው ኪዮ “ይህን ያገኘሁት በእናንተ ምክንያት ነው” በማለት በጃፓን ለሚገኘው የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ቅርንጫፍ ቢሮ ጻፈች። እንዲህ ያለ ከፍተኛ ምስጋና የጻፈችበት ምክንያት ምንድን ነው? ኪዮ በቅርቡ የጃፓን የትራፊክ ደኅንነት ማኅበር ባዘጋጀው አገር አቀፍ የድርሰት አጻጻፍ ውድድር ላይ አሸናፊ ሆናለች። ውድ የሆነው ሽልማት ወደ ስዊድን ለጉብኝት መጓዝንም ይጨምራል።
ኪዮ በመጠበቂያ ግንብ የመጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር ለሚዘጋጁት ብዛት ያላቸው ጥሩ ጥሩ ጽሑፎች አድናቆቷን ለመግለጽ ደብዳቤ ጻፈች። ጽሑፎቹ በውድድሩ እንድታሸንፍ በጣም እንደረዷት ይሰማታል። ከዚህ ውድድር ሌላ ትምህርት ቤቷን በመወከል በብዙ የንግግሮችና የድርሰት አጻጻፍ ውድድሮች ላይ ተካፍላለች። “በአብዛኞቹ በእነዚህ ውድድሮች ላይ ርዕሱ ይሰጣል። ተማሪዎቹም በመጻሕፍት ቤት ውስጥ ለድርሰቶቻቸው የሚሆን ምርምር ያደርጋሉ። ይሁን እንጂ እኔ እዚህ ሁሉ ችግር ውስጥ አልገባም። እቤት በመጻሕፍት መደርደሪያው ላይ አስደናቂ ጽሑፍ አገኛለሁ!” አለች። ቀጥላም “የተሰጠው ርዕስ ምንም ይሁን ምን ስለ እርጅና ችግሮች ይሁን፣ ስለ አካባቢ፣ ስለ ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ይሁን ወይም ራስን ስለማሻሻል አብዛኛውን ጊዜ በመጠበቂያ ግንብ ወይም በንቁ! መጽሔት ላይ ይህን በተመለከተ የተሰጠ ጥልቅ ማብራሪያ ይኖራል።”
ሆኖም ኪዮን የረዷት ጽሑፎቹ ብቻ አይደሉም። በይሖዋ ምስክሮች የትምህርት መስጫ ፕሮግራም ላይ ያገኘችው ትምህርት የንባብና የመጻፍ ችሎታዋን እንድታሻሽል ረድቷታል። ይህም በውድድሮቹ ላይ ብልጫ እንድታገኝ አስችሏታል። “በአንድ ወቅት ላይ በዩኒቨርሲቲ ገብቼ ለመማር እፈልግ ነበር። ነገር ግን ይህን የመሰለ ማሰልጠኛ ከየት ላገኝ እችላለሁ?” ስትል አመነች። አሁን እሷ ካገኘችው ትምህርት ሌሎችም ተጠቃሚዎች እንዲሆኑ ለመርዳት በሙሉ ጊዜ ለመሥራት ተስፋ ታደርጋለች። ኪዮ በድርሰት አጻጻፍ በውድድሩ ባገኘችው ሽልማት ብትደሰትም ልቧ የሕይወትን ሽልማት በማግኘቱ ላይ አተኩሯል።—ከፊልጵስዩስ 3:14 ጋር አወዳድር።